የጌዴኦ ዞን ዜና
-
የጌደኦ ዞን ከፍተኛ አመራሮች በወቅታዊ ሀገራዊና አለማቀፋዊ ሁኔታ ያካሄዱት የምክክር መድረክ በመሠረታዊ ሀሳቦች መግባባት በመፍጠር ተጠናቋል። መድረኩን የመሩት የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) አመራሩ መረጃ ተኮር ተግባቦትን ከህብረተሰቡ ጋር በመፍጠርና ጤናማ ማህበራዊ መስተጋብር በመፍጠር በተሳሳቱ መረጃዎች ህብረተሰቡ እንዳይሸበር የማድረግ ድርብ ኃላፊነት አለበት ብለዋል። አያይዘውም የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ስሜት ኮርኳሪ አጀንዳዎችን ወደ ህዝቡ በመርጨት ተግባር የተሰማሪፉ አካላትም መኖራቸውን በውል በመገንዘብ አስፈላጊውን የአጸፋ ሥራ መስራት የአመራሩ ቁልፍ ተግባር እንደሆነም ጠቁመዋል። አሁን ላይ በአለማቀፍ ደረጃ በተለይም በመካከለኛ ምስራቅ፣ አሜሪካና እስራኤል መካከል እየተፈጠረ ያለ ሁኔታ የሚያልፍና ጊዜያዊም ቢሆን መሠረታዊ ጉዳቶችን እያስከተለ ይገኛል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው ሀገር-በቀል የሆኑ የአካባቢ ግብርና ሥራዎች በቅርበት በመደገፍ አርሶ አደሩን በማበረታታት እና ሌሎች ተግባራትን በማከናወን ያስፈልጋልም ብለዋል። የጌዴኦ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊና ዋና የመንግስት ተጠሪ ኢንጂነር ተመስገን ጥላሁን በበኩላቸው የብልጽግና አመራር እንደመሆናችን ፈተናዎችን ወደ እድል ቀይሮ የመንቀሳቀስ እስትራቴጂ በመከተል የህዝቡን ተጠቃሚነትንና ብሔራዊ ጥቅም መሠረት ያደረገ አማራጮችን በመከተል ወቅታዊውን አለማቀፍ ሁኔታ ማለፍ እንደሚገባ ተናግረዋል። በመድረኩ የተሳተፉ ከፍተኛ አመራሮችም የወቅቱን ሀገር አቀፍ እና አለምአቀፋዊ ሁኔታ በመገንዘብ፣ ዝግጁ በመሆን የሀገሪቷን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ የሚያስችሉ ስትራቴጂካዊ የመሻገር አቅጣጫዎችን በቁርጠኝነት እንደሚተገብሩ ገልጸዋል።
April 22, 2026

